|
የቅንጅት አባላት በእሥር ቤት ውስጥ መሞታቸው ተገለጠ |
|
|
|
Monday, 07 July 2008 |
|
ሶስት የቅንጅት አባላት በእሥር ቤት ውስጥ
መሞታቸው ተገለጠ፡፡
በአዊ ዞን ውስጥ ነዋሪ የነበሩ ሶስት የቅንጅት ለአንድነትና ለዴሞክራሲ ፓርቲ አባላት በከፍተኛ ድብደባ እንዲሁም በመጥፎ አያያዝ በልዩ ልዩ እሥር ቤቶች ውስጥ መሞታቸውን የመረጃ ምንጮች ሰሞኑን ገለጡ፡፡
እንደ ምንጮቹ አገላለፅ በዚህ ሁኔታ ለሞት የተዳረጉት የመቶ አለቃ አርጋታ ጎበናና አቶ ስሜነህ ዓለሙ የፓርቲው የወረዳ ኮሚቴዎች ሰብሳቢዎች የነበሩ ሲሆኑ እንዲሁም አቶ ፀጋዬ አየለ የተባሉ አባል መሆናቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡
በተጨማሪም ጥላሁን አየሌው የተባሉ የወረዳ ኮሚቴ ሰብሳቢ በወያኔ እጅ ከወደቁበት ቀን አንሥቶ የት እንደ ደረሱ የማይታወቅ ሲሆን እንዲሁም ከበበው አያሌው ሌላው የቅንጅት ፓርቲ አባል ከቤት ንብረታቸው ተፈናቅለው በስደት እንዲኖሩ መገደዳቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡
በተመሣሣይ መልኩ በዚህ ዞን ውስጥ ብዙ ንፁሃን ዜጎች በፖለቲካ አመለካከታቸው ብቻ በድብደባ አካለ ጎደሎ ሊሆኑ እንደቻሉ መረጃዎች አመልክተዋል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ በዚሁ በአዊ ዞን በዳንግላ፤ በቲሊላ፤ በአንጅባራና በአንካሻ ወረዳዎች ውስጥ የትምህርት ፖሊሲን በመቃወም ሰልፍ ከወጡ ተማሪዎች መካከል ብዙዎች ተይዘው የታሰሩ ሲሆን አበባው ዕርቅይሁን የተባሉ መምህር ደግሞ ክፉኛ ተደብድበው ሆስፒታል ገብተው መሞታቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡
በዚሁ ሕዝቡም ጭምር በተሳተፈበት ሰላማዊ ሰልፍ ላይ ብዙ ሰዎች የተደበደቡ ሲሆን መንገዶች ተዘግተው የትራፊክ እንቅስቃሴም ታውኮ እንደነበር ተውቋል፡፡
|