|
በአርባ ምንጭ የሁለት ደብሮች አስተዳዳሪ ታሰሩ |
|
|
|
Monday, 04 August 2008 |
|
በጋሞ ዞን በአርባ ምንጭ ከተማ የመንበረ ቅዱስ ሚካኤልና ገብርኤል ደብሮች አስተዳዳሪ አባ ኃይለሚካኤል ታደሰ በዞኑ ፖሊስ መምሪያ ከሐምሌ 23 ቀን 2ዐዐዐ ዓ.ም አንሥቶ በእሥር ላይ እንደሚገኙ ሰሞኑን ምንጮች ከአርባ ምንጭ አስታውቀዋል፡፡
አስተዳዳሪው የታሰሩበት ምከንያት ምን እንደሆነ ከአገዛዝ አካላት ያልተገለፀ ሲሆን አንዳንድ የአርባ ምንጭ ነዋሪዎች እኚህ የሐይማኖት አባት በሐዝብ ዘንድ ተወዳጅ በመሆናቸው ብቻ እንዲሁ ሰበብ ተፈልጎ የታሰሩ መሆናቸውን ሲናገሩ መደመጣቸውንም ምንጮች አክለው ገልፀዋል፡፡
አባ ኃይለሚካኤል በግልፅ ተለይቶ በጭብጥ የተመለከተ የክስ ቻርጅ ባይደርሳቸውም ፍርድ ቤት ቀርበው ወደ ማረፊያ ቤት የተመለሱ መሆናቸውን ምንጮች አስረድተዋል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ በአርባ ምንጭ ከተማ ነዋሪ የሆኑት 1 አብዮት አጌና 2. አንዱዓለም አጌና 3. ባንትይርጉ በገራ 4. ሰሎሞን ተካልኝ 5. ዓለማየሁ ጌታ እንዲሁም 6. ይርጋዓለም ታፈሰ የተባሉ ግለሰቦች ከሐምሌ 21 ቀን 2ዐዐዐ ዓ.ም አንሥቶ በእሥር ላይ እንደሚገኙ ምንጮች ከአርባ ምንጭ አመለከቱ፡፡
እንደ ምንጮቹ አገላለፅ ግለሰቦቹ ተይዘው ሊታሰሩ የበቁት "የከተማውን ሀብረተሰብ ለዐመፅ አነሣሥታችኋል" በሚል ሰበብ ሲሆን ከተሰሩበት ወቅት አንሥቶ አስከካሁን ፍርድ ቤት አለመቅረባቸውንም ለማወቅ ተችሏል፡፡
|