|
በኢትዮጵያ ምድር መንግስት መኖሩን አምናለሁ፡፡ ሕግ ለመኖሩ ግን በጣም እጠራጠራለሁ፡፡ ሕግ ከሌለ ደግሞ የኢትዮጵያ መንግስት ስርዓተ አልባ አገዛዝ እንደሚያራምድ አፌን ሞልቼ ለመናገር በተጠየቅ እደገፋለሁ፡፡ ዕውነት እውነት አላችኋለሁ፡፡ ከሀሰት ለማትረፍ ከቶም ፍላጎት አጣለሁ፡፡ የጥቃቱ ሰለባ ነኝ፡፡ ይህ ዕውነት ነው ! ቃሌ ሐቅ ነው! እነሆ!
ዕለቱ ማክሰኞ ነው፡፡ ጥቅምት 18 ቀን 2001 ዓ.ም መሆኑን ደግሞ እንመዝግብ! ከምሽቱ 6፡30 ሆኗል፡፡ ጥቃቱ የተፈፀመብኝ በሶዶ ከተማ ውስጥ ነው፡፡ አሁን በወላይታ ሶዶ ከተማ በውበት ሆቴል ቤት በቁጥር 25 መኝታ ክፍል ውስጥ በጀርባዬ ተንጋልዬ የቀን ውሎዬን ሂሳብ አወራርዳለሁ፡፡ አወጣለሁ፡፡ አወርዳለሁ፡፡ ለመስክ ጉዞዬ በዕቅድ ከተያዙት ዞኖች መካከል ሐዲያ ፤ ከምባታና ዝዋይ ልዩ ዞን ይቀራሉ፡፡ አርባ ምንጭ ፤ ጂንካ ፤ ሳውላና ዋካ ሔጄ ተመልሼአለሁ፡፡ ጉዞዬ የተሳካ ነበር፡፡ በማግስቱ ሐዲያ ለመሔድ ዕቅድ ይዤአለሁ፡፡ ሀገር ሰላም መስሎኝ በሰላም ተኝቼአለሁ፡፡ መብራት አላጠፋሁም፡፡ ሐሳብ አድማስ የለውም ፡፡ ማን ይከለክለኛል?ለመስክ ስራ ተመድቤ ከወጣሁበት ከ28-1-2001 አንስቶ ያጋጠሙኝን ነገሮች ሁሉ አስታውሳለሁ፡፡ ጂንካ የከንቲባ ጽ/ቤት በፓሊስ አስጠርቶኝ ለግማሽ ሰዓት በቁጥጥሩ ሥር አቆይቶኛል፡፡ ቀላል ክስተት በመሆኑ አላማረርሁም፡፡ አሁንም በዚሁ በጂንካ የደቡብ ኦሞ ፖሊስ አዛዥ ከሌሎች የስራ ባልደረቦቹ ጋር በመሆን ጠርቶኝ የጦር መሳሪያ መያዝ አለመያዜን ጠይቆኛል፡፡ ተገቢውን መልስ ሰጥቼው ተለያየን፡፡ የተካረረ ነገር አልተፈጠረም፡፡
አሁን ግን የባሰ ነገር እየመጣ ነው! ልብ በሉ ! ያለሁት በሶዶ ከተማ ውስጥ ነው! አንድ ! ሁለት! አንድ! ሁለት! አንድ! ሁለት! አሁን ፀጥታ ነው! የሆቴል ቤቱ ሙዚቃ ከግማሽ ሰዓት በፊት አፉን ዘግቷል፡፡ ድምፅ የለም! ዕንቅልፍ ባይወስደኝም የዕንቅልፍ ሰዓት መሆኑን አንጣ ! አንድ ! ሁለት! አንድ! ሁለት! አሁን ያቺ መጥፎ ሰዓት በጣም ቀርባለች ፡፡ አንድ ! ልብ በሉ ! ያቺ ሰዓት እየቀረበች ነው! ሁለት ! በጣም ቀርባለች ! ሦ-ሦ-ሦ ሦስት ! ኳ! ኳ! ኳ!
ማነህ?
እኛ ነን! የግቢ ዘበኞች ነን!
ምን ፈለጋችሁ?
ጋሼ! እንግዶች ሁሉ መታወቂያቸውን እያስመዘገቡ በመሆኑ እርስዎም እባክዎን ያስመዝግቡ!
ምንም አልጠረጠርሁም ፡፡ ዘበኛውን በድምፅ ለይቼ አውቄዋለሁ፡፡ አዲሱ የተባለ ዘበኛ ነው፡፡ ተነስቼ ከፈትኩለት፡፡
እንዴት ልጠረጥር እችላለሁ! መታወቂያ መመዝገብ ነባር አሰራር ነው፡፡ በተዛመደ መልኩ ተከራይ በዚያ ሆቴል ቤት ለምን ያህል ጊዜ እንደሚቆይ በቅፁ ላይ ይሞላል፡፡ ይህ በሆቴል ቤቶች የተለመደ አሰራር መሆኑን አውቃለሁ፡፡ በዚህ ዕውነታ ተመርቼአለሁ፡፡ ግን ተሳስቼአለሁ፡፡ ከመንግስት በስተቀር ሕግ አለመኖሩን ዘንግቼአለሁ፡፡ በሩን እንደ ከፊትሁ ሁለት ፖሊሶች ዘው ብለው ገቡ፡፡ስድስት ፖሊሶች የጦር መሳሪያና ዱላ ይዘው ደጅ ቆመዋል፡፡ ወደ ውስጥ ከገቡት አንዱ መታወቂያ ጠየቀኝ ፡፡ አላቅማማሁም፡፡ ተዛማጅ ማስረጃዎቼንም አሳየሁት፡፡ ግን ሊቀበለኝ ፍቃደኛ አልነበረም፡፡ ከዚያች ደቂቃ አንስቶ እስረኛ መሆኔን ነገረኝ፡፡ ዕዳ ከሜዳ ! ዱብ ዕዳ ወረደ ፡፡ አንደኛው ሰነዶቼን እያነሳ ለሌላኛው ፖሊስ ሊያቀብል ገባ፡፡ ባወግዘውም ስሚ አጣሁ፡፡ ደጅ የቆሙት ሊመቱኝ አስፍስፈዋል፡፡
ገፈታትረው ወደ ውጭ አስወጡኝ፡፡ ሰነዶቼን ሁሉ ዘርፈው ይዘዋል፡፡ እነሱ ስምንት ሲሆኑ እኔ አንድ ነኝ፡፡ ምንም ለማድረግ አቅም አልነበረኝም ፡፡ አንደኛው ፖሊስ የመቶ አለቃ ጆቢር ሶርሳ ይባላል፡፡ ሌላው ፖሊስ መንገሻ መሆኑ ተነግሮኛል፡፡ የመቶ አለቃው ከጌታው ጋር በሞባይል ለጥቂት ደቂቃዎች ተነጋገረ፡፡ ሁሉም ተያዩ፡፡ አሁን የመቶ አለቃው ሐሳቡን ለወጠ፡፡ ተመልሼ ወደ መኝታ ክፍሌ እንድገባ አዘዘኝ፡፡ በጣም ብዙ የፓርቲዬንና የግል ሠነዶቼን ተዘረፍሁ፡፡ ሕግ የለም ! ለማን አቤት ይባላል? ፖሊስ ዘረፈኝ! ገዥው ፓርቲ ያዘዛቸው አገልጋዮች ዘበኛውን በገንዘብ ገዝተው መኝታ ቤቴን አስከፍተው ዘረፉኝ ፡፡ ሕግ ቢኖርም ባይኖርም ግን ከስሼ አስመስክሬአለሁ፡፡ ወጤቱ ምን ሊሆን ይችላል? እንገምት እስቲ!
ተከሳሽ ..................................ገብረ መድህን
መርማሪ ፖሊስ.........................በረሔ
አቃቤ ሕግ...............................ሐጎስ
ዳኛ........................................ገብረ እግዚ
ፍርዱ ምን ሊሆን ይችላል ?
|